የማህበራዊ ልማት እመርታ ለሀገር ግንባታ’’ በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀውና በማህበራዊ ዘርፍ ባለፉት ዓመታት የተመዘገቡ ዐበይት ውጤቶች የቀረቡበት የምክክር መድረክ፤ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ተካሂዷል።
በዚህም ባለፉት ዓመታት በማህበራዊ ዘርፎች የተመዘገቡ ወሳኝ ስኬቶች ቀርበዋል።
በስምንት የለውጥ ዓመታት፤ ኢትዮጵያ በመሰረታዊና ማህበራዊ ዘርፎች የተስተዋሉ ክፍተቶች ላይ ትኩረት በማድረግ፤ በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ሰፊ ሥርዓታዊ ሽግግር አድርጋለች።
በትምህርት ዘርፍ አዲስ ሥርዓተ-ትምህርትን በመተግበር፣ የመማሪያ መጽሐፍት ስርጭትን በማሻሻል እንዲሁም የከፍተኛ ትምህርትና የሀገር አቀፍ ፈተና ሥርዓቶችን በማዘመን፣ የትምህርት ዘርፉ ጥራትና ተዓማኒነት እንዲላበስ ተደርጓል።
በተመሳሳይ የጤናው ዘርፍ ለ30 ዓመታት የቆየውን ፖሊሲ በመከለስ፤ ከመከላከል ጎን ለጎን አክሞ የማዳን አገልግሎት ላይ ትኩረት የተደረገ ሲሆን፣ በዲጂታል ጤና፣ በሀገር ውስጥ የፋይናንስ ምንጭና በጤና ዲፕሎማሲ ረገድ ጉልህ ውጤቶች ተመዝግበዋል።
የኢኮኖሚና ማህበራዊ አቅምን የመገንባት ስራዎችም በተመሳሳይ መልኩ ውጤታማ ናቸው። የሥራና ክህሎት ዘርፉ የቴክኒክና ሙያ ትምህርትና ሥልጠናን (TVET) በማዘመንና የቢዝነስ ማጠናከሪያ ማዕከላትን ማስፋፋት፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የሥራ ስምሪት ከ19.8 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የሥራ ዕድል መፍጠር ተችሏል።
በዚህ አካታችነትን ባማከለ ስኬት፣ በሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ዘርፍም የተደገመ ሲሆን፣ 26.8 ሚሊዮን ሴቶችንና 4.3 ሚሊዮን ወጣቶችን በኢኮኖሚ እና በፖለቲካ ተሳትፎ ተጠቃሚ ከማድረግ ባለፈ ለተጋላጭ ዜጎችና በአደጋ ለተጎዱ ወገኖች የተሻለ ጥበቃ እንዲደረግ አስችሏል።
በባህልና ስፖርት ዘርፉም፤ የሀገሪቱን ቅርሶች ለብሔራዊ አንድነትና ለዲፕሎማሲ ስኬት እንዲውሉ በማድረግ ረገድ ትልቅ ሚና ተጫውቷል። ከእነዚህም መካከል 83 የአደባባይ ክብረ በዓላት እውቅና ማግኘታቸው፣ 36 የባህል ማዕከላት መገንባታቸው እንዲሁም አደይ አበባ ስታዲየምን ጨምሮ ከመቶ ሺህ በላይ አዳዲስ የስፖርት መሠረተ ልማቶች መገንባታቸው የዘርፉ ጉልህ ስኬቶች ናቸው።
በአጠቃላይ በዘርፎቹ የተመዘገቡ ለውጦች፤ መንግሥት ለተቋም ግንባታ፣ ለዲጂታል ሽግግርና ለሰው ሀብት ልማት ያለውን ቁርጠኝነት የሚያሳዩ ናቸው።
ለተጨማሪ የመረጃ አማራጮች
https://linktr.ee/FDREGovermentCommunication














