“የዓድዋ ትሩፋት አፍሪካዊያን የጋራ ራዕይን ሰንቆ እንዲተጉ ያደረገ ድል ነው”

129ኛው የዓድዋ ድል በዓል በድምቀት ተከበረ

የካቲት 23 ቀን 2017 ዓ.ም

ታሪካዊዉ የዘንድሮ የዓድዋ ድል በዓል፣ “ዓድዋ የጥቁር ህዝቦች ድል” በሚል መሪ ቃል የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ታዬ አጽቀስላሴ፣ የመከላከያ ሚኒስትር ኢ/ር አይሻ መሐመድ እና የቀድሞው የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር ሙሳ ፋኪ ማህማትን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፤ አርበኞች፣ የመከላከያና የፀጥታ አካላት አመራሮች፣ ዲፕሎማቶችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በዓድዋ ድል መታሰቢያ ሙዚየም በድምቀት ተከብሯል።

የኢፌዴሪ ፕሬዚዳንት ታየ አጽቀስላሴ በዓሉ ላይ ባደረጉት ንግግር፣ የዓድዋ ድል በዓለም ለሰው ልጆች ሁሉ ሰብዓዊ ክብርን ያጎናጸፈ እና የኢትዮጵያውያንን ጅግንነት ለዓለም ያስመሰከረ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡ የድሉ መነሻችዎችና ዉጤቶችም በትውልዱ ሊመረመር፣ እንዲሁም ሊጠበቅ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

የኢፌድሪ መከላከያ ሚኒስትር ኢንጅነር አይሻ መሐመድ በበኩላቸው፤ እለቱን በማስመልከት የመክፈቻና የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

በዚህም ዓድዋ የኢትዮጵያውያን ጽናትና አልበገር ባይነት ማሳያ ከመሆኑም ባሻገር የመላው ጥቁር ህዝቦች ድል መሆኑን ተናግረዋል። ጀግንነት የመላው ኢትዮጵያውያን የጋራ እሴት የተደረገበት፣ እጅግ ከፍተኛ የውጊያ ጥበብ የታየበት መሆኑንም ኢንጅነር አይሻ አስታዉሰዋል፡፡

አያይዘውም ዓድዋ የድል ታሪክ ብቻ ሳይሆን የአባቶቻችንን ህልም አንድነታችንንና ብልፅግናችንን በማረጋገጥ ከግቡ ማድረስ እንዲሚቻል የሚያሳይ ነዉ ብለዋል።

የኢፌድሪ የጦር ሀይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ባስተላለፉት መልዕክት፣ የዓድዋ ድል የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የጥቁር ህዝቦች ድል ነዉ ብለዋል፡፡ ጀግኖች አባቶች ኢትዮጵያን ለመጠበቅና ለማቆየት ብዙ መስዋእትነትን ከፈለዋል፤ የአሁኑ ትዉልድ ደግሞ የሀገሪቱን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ በጋራ መስራትና መቆም እንዳለበት መሳያ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

የቀድሞው የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀ-መንበር ሙሳ ፋኪ ማህማት በበኩላቸዉ፣ የዓድዋ ድል ጦርነትን የማሸነፍ ታሪክ ብቻ ሳይሆን በአፍሪካዊያን ዘንድ አንድነትና የጋራ ራዕይ እንዲሰነቅ፣ እንዲሁም ለዉጤት እንዲበቃ ያደረገ የጥቁር ህዝቦች ኩራት መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የዓድዋ ድል በአንድነትና በትብብር የአፍሪካዊያንን የመልማት ፍላጎት እዉን ማድረግ፣ በአህጉሪቱ ሰላምና ጸጥታን ማስፈን እንደሚቻል ጥሩ ማሳያ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ልማት፣ ሁለንተናዊ ሰላም፣ ዲሞክራሲ እና ነፃነት ተምሳሌት መሆኗን ያነሱት ሙሳ ፋኪ፣ በገጠርና በተለያዩ የሀገሪቱ ከተሞች እየተሰሩና በመሰራት ላይ ያሉ ዜጋ ተኮር የልማት ስራዎችንም አድንቀዋል፡፡

Similar Posts