የሚኒስትሮች ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 47ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ፡፡ (ግንቦት 28 ቀን 2017 ዓ.ም፣ አዲስ አበባ)

የሚኒስትሮች ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 47ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ፡፡ በዚህም መሰረት፦

1. 2018 ዓ.ም የፌዴራል መንግስት በጀት በአስር ዓመቱ መሪ የልማት ዕቅድ ላይ የተቀመጡ ግቦችን ከማስፈጸም፤ የሀገር ደህንነትን ከማስጠበቅ፣ ምርትና ምርታማነትን ከማሳደግ፣ በተፈጥሮና ሠው ሠራሽ ችግሮች ምክንያት የተፈናቀሉ ዜጎችን ከመርዳት አንጻር፤ የ2018-2022 የመካከለኛ ዘመን የማክሮ ኢኮኖሚና ፊስካል ማዕቀፍን መሠረት በማድረግ እና የ2017 በጀት ዓመት የፕሮግራም በጀት አፈጻጸምን በመገምገም ተዘጋጅቶ የቀረበ ነው፡፡ በዚሁ መሠረትም ለፌዴራል መንግስት መደበኛ ወጪዎች፣ ለካፒታል ወጪዎች፣ ለክልሎች የሚሰጥ ድጋፍ እና ለዘላቂ የልማት ግቦች ማስፈጸሚያ ድጋፍ ወደ ሁለት ትሪሊዮን የሚጠጋ በጀት ለምክር ቤቱ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በቀረበው የፌዴራል መንግስት የ2018 ረቂቅ በጀት አዋጅ ላይ ከተወያየ በኋላ ግብአቶችን በማከል ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡

2. የስታርታፕ ምህዳርን በመፍጠር ስታርታፖች የሚመሰረቱበት፣ የሚንቀሳቀሱበትና የሚያድጉበት እና ቴክኖሎጂን ተግባራዊ በማድረግ አዳዲስ ምርቶችን የሚያመርቱበትና አገልግሎቶችን የሚሰጡበት እንዲሁም በዘርፉ የፋይናንስ አቅርቦት ችግሮችን ለመፍታት እንዲያስችል ሆኖ ረቂቅ አዋጁ ተዘጋጅቶ ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በአዋጁ ላይ ከተወያየ በኋላ ወደ ህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡

Similar Posts