የ100 ቀናት ግምገማ እና የ9 ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት:-
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በተገኙበት በዛሬው ዕለት በቀረበው የ100 ቀናት ግምገማ እና የ9 ወራት የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት፣ የፕላንና ልማት ሚኒስትር ዶ/ር ፍጹም አሰፋ ቁልፍ ማሻሻያዎችንና የተመዘገቡ ስኬቶችን አብራርተዋል።
ሪፖርቱ ቀደም ሲል ደካማ ተቋማዊ አቅም፣ ዝቅተኛ ምርታማነት፣ ውስን የግል ዘርፍ ተሳትፎ እና ውጤታማ ያልሆኑ የመንግሥት የልማት ድርጅቶች ይስተዋሉበት በነበረው አስቸጋሪ የኢኮኖሚ ሁኔታ ውስጥ የተከናወኑ ተግባራትን ያካተተ ነው። መንግሥት ለእነዚህ ተግዳሮቶች ምላሽ ለመስጠት ኢኮኖሚውን ለውድድር ክፍት ማድረግን፣ ሀገር በቀል ፖሊሲዎችን ማራመድ እና በተለያዩ ዘርፎች እድገትን ማዕከል ያደረገ ተጨባጭ የሪፎርም አጀንዳ ተግባራዊ አድርጓል።
ይህም በካፒታል ገበያ ልማት፣ በመንግሥትና በግል እንዲሁም በመንግሥትና በሕዝብ አጋርነት በተዘረጉ አዳዲስ የፋይናንስ ሥርዓቶች የታገዘ ሲሆን፤ በተቀናጀ የክትትል ሥርዓት እና ፈጣን የፕሮጀክት አፈጻጸም አማካኝነት የኢኮኖሚ አስተዳደር እንዲጠናከር ተደርጓል።
በዚህ ለውጥ ውስጥ የግሉ ዘርፍ ለኢኮኖሚ ዕድገት ቁልፍ ሞተር እንዲሆን ትልቅ ትኩረት የተሰጠው ሲሆን፣ ይህም በጠንካራ የልማት አጋርነትና በስራ ላይ ባለው የዕዳ ሽግሽግ (debt restructuring) የተደገፈ ነው።
በተመሳሳይ የተቋማዊ ሪፎርም፣ የማኅበራዊ አካታችነት እና የአገልግሎት አሰጣጥ ማሻሻያ ሥራዎች ተደራሽነትን ለማስፋት፣ ጥራትን ለማረጋገጥና የአስተዳደር መዋቅሮችን ለማጠናከር አልመው ተከናውነዋል። በዓለም አቀፍ ደረጃ ደግሞ ዜጋ ተኮርና ንቁ ዲፕሎማሲ ቀጣናዊ ትስስርን እና የኢትዮጵያን ተሰሚነት አሳድጓል። የብሪክስ (BRICS+) አባልነት፣ በንግድና ኢንቨስትመንት ላይ ያተኮሩ አጋርነቶች መስፋፋት፣ በአየር ንብረት ዲፕሎማሲ የታየው መሪነት እና የኮፕ 32 (COP32) ጉባኤን ለማስተናገድ የተመረጠችበት ስኬት እንዲሁም የባሕር በር ለማግኘት የሚደረገው ጥረት ተጠቃሽ ስኬቶች ናቸው። እነዚህ ማሻሻያዎች ወደ ተጨባጭ የኢኮኖሚ ውጤቶች ተቀይረዋል።
በአሁኑ ወቅት የኢኮኖሚ ዕድገቱ 9.2 በመቶ የደረሰ ሲሆን ወደ 10.2 በመቶ እንደሚያድግ ይጠበቃል። ባለፉት ስምንት ዓመታትም በአማካይ 7.5 በመቶ ዕድገት ተመዝግቧል። የኢንቨስትመንት ከባቢው በከፍተኛ ሁኔታ መሻሻሉን ተከትሎ 2,153 የኢንቨስትመንት ፈቃዶች የተሰጡ ሲሆን (65 በመቶው በማምረቻ ዘርፍ ነው)፤ የመንግሥት የልማት ድርጅቶችም ከነበሩበት የ8 ቢሊዮን ብር ኪሳራ ወጥተው ባለፉት ዘጠኝ ወራት 2.1 ትሪሊዮን ብር ገቢ ማስገኘት ችለዋል። በዚሁ የዘጠኝ ወራት ውስጥ ወደ 96,000 የሚጠጉ የሥራ ዕድሎች ተፈጥሯል።
የዘርፍ አፈጻጸምን በተመለከተ የግብርና ሜካናይዜሽን ማደግ፣ የማምረቻ ዘርፍ የገበያ ድርሻ ከ25 ወደ 46 በመቶ ከፍ ማለቱ፣ የወርቅ ኤክስፖርት በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩ፣ የቱሪዝም ኢንቨስትመንትና መዳረሻዎች መስፋፋት እንዲሁም በ4ጂ (4G) እና 5ጂ (5G) ኔትወርክ ዝርጋታ፣ በዲጂታል የመንግሥት አገልግሎቶችና በአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ (AI) ተቋማት አማካኝነት የታየው ፈጣን የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን በሪፖርቱ ተመላክቷል።
በተጨማሪም በአረንጓዴ ልማትና በአየር ንብረት ለውጥ መቋቋም ረገድ በአካባቢ ጥበቃ፣ በልቀቃ ቅነሳ እና የአየር ንብረት ለውጥን በሚቋቋም ግብርና ላይ እድገት ታይቷል። የሰብዓዊ ድጋፍ ሥርዓቱም የአደጋ ስጋት ክምችት አቅምን በማሳደግ፣ የመጋዘን መሠረተ ልማትን በማስፋፋት፣ የቅድመ ማስጠንቀቂያና ድንገተኛ ምላሽ አሰጣጥን በማሻሻል እንዲሁም የሕዝብ ተሳትፎን በመጨመር እንዲጠናከር ተደርጓል።
በአጠቃላይ የሪፖርቱ ግምገማ በመዋቅራዊ ለውጥ፣ በዘርፍ ትራንስፎርሜሽን እና በጠነከረ ዓለም አቀፋዊ ተሳትፎ ላይ የተመሠረተ ተወዳዳሪ፣ አካታች እና የማይበገር ኢኮኖሚ ለመገንባት እየተደረገ ያለውን ተጨባጭ መሻሻል አመላክቷል።
